የሐዘን መግለጫ ከኢትዮያ ስፖርት ፌደሬሽን በሰሜን አሜሪካ

የኢትዮጵያ ስፖርት ፌዴሬሽን በሰሜን አሜሪካ በመጀመርያው የፌዴሬሽኑ ፕሬዚደንት በአቶ ፍስሃ ወልደአማኑኤል ዜና ዕረፍት የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን እንገልፃለን::

የኢትዮጵያ ስፖርት ፌዴሬሽን በሰሜን አሜሪካ በመጀመርያው የፌዴሬሽኑ ፕሬዚደንት በአቶ ፍስሃ ወልደአማኑኤል ዜና ዕረፍት የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን እንገልፃለን::

ፌዴሬሽናችን የድርጅት ቅርፁን በያዘበት በ1985 ጋሽ ፍስሃ የመጀመሪያው የፌዴሬሽኑ ፕሬዚደንት ሆኖ ተመርጦ ነበር:: ከ1985 ጀምሮ ለቀጠሉት ለ፵፪ አመታት ያለማቋረጥ በፌዴሬሽኑ አመታዊ በአል ላይ ተገኝቷል:: በ2026 በአላችን ላይ በህመም ምክንያት ሊገኝ ባለመቻሉ አለመኖሩ አጉድሎ ነበር::

የፕሬዚደንትነቱን ሃላፊነት ሲጨርስ በፌዴሬሽኑ የእግር ኳስ ውድድር ክፍል ውስጥ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል ከ35 አመታት በላይ በበጎ ፈቃደኝነት አገልግሏል! ጋሽ ፍስሃ "በጎ ስራ የህይወት ስንቅ ነው" ሲል አድርጎትና ኖሮት ስለሆነ ከትክክለኛው ሰው: ትክክለኛው ቁምነገር እንደሆነ የፌዴሬሽኑ ቤተሠብ በሙሉ ይረዳዋል::

ጋሽ ፍስሃ ወልደአማኑኤል ከሐረር ከተማ ወጣ ከምትል ደደር ከምትባል ትንሽ ቀበሌ ነው የተወለደው:: እስከ ስድስት አመቱ ያደገና የተማረው ሐረር ነው:: ከልጅነቱ ጀምሮ በኳስ ፍቅር ተከትቧል:: ቤተሰቡ ወደ አዲስ አበባ ሲዛወር በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት እየተማረ ነበር በቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ቡድን ተመልምሎ መጫወት የጀመረው:: ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር የአዲስ አበባ እና የኢትዮጵያ ሻምፕዮናን ደጋግሞ አሸንፏል:: በብሄራዊ ቡድን ደግሞ ከ4ኛ እስከ 7ኛ የአፍሪካ ዋንጫ አገሩን ወክሎ ተጫውቷል:: አንዳንዶቹን ከአሜሪካን አገር እየተመለሰ ነበር የተጫወታቸው:: ጋሽ ፍስሃ በከረረ የሩቅ ምቶቹ ስለሚታወቅ "መድፈኛው": እጅግ ጥበበኛ ተጫዋች ስለነበረ ደግሞ "ኳስ ፊደሉ" የሚሉ ቅጽል ስሞች ነበሩት::

እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1969 በእግር ኳስ ስኮላርሺፕ ዩኒቨርስቲ ኦፍ ካሊፎርኒያ ሎስ አንጀለስ (UCLA) መጣ:: በዚያ ቡድን ውስጥ ከኢትዮጵያ ጀምሮ አብረውት የተማሩና የተጫወቱ እነ ሸዋንግዛ አጎናፍር: ተቀዳ አለሙ: ሰለሞን ተርፋ እና ሌሎችም ድንቅና ታዋቂ ተጫዋቾች ነበሩ::

ጋሽ ፍስሃ በዩኒቨርስቲ የጀመረውን ብቃት በፕሮፌሽናልነት ቀጥሎበት የMajor League Soccer (MLS) ቀዳሚ በነበረውና እነፔሌ በሚጫወቱበት ሊግ ውስጥ ለሎስ አንጀለስ አዝቴካ ቡድን ከታዋቂው እንግሊዛዊ ጆርጅ ቤስት ጋር በአንድ ቡድን ተጫውቷል:: እንደባላጋራ ደግሞ ከእነፔሌ: የጀርመኑ ሄንዝ ቤክንባወር እና ጌርድ ሙለር: የፖርቱጋሉ ኢዞቢዮ: የኔዘርላንዱ ዦአን ክሩይፍ ጋር ተጫውቷል::

ጋሽ ፍስሃ ከእግር ኳሱ ጎን ትምህርቱን ቀጥሎ ከUCLA በባችለር ከሁለት ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ የተለያዩ ሁለት የማስተርስ ዲግሪ ድረስ ተምሯል::

በ1978 በሎስ አንጀለስ ከተማ ኢትዮጵያውያንን በማስተባበር የመጀመሪያውን የሎስ አንጀለስ ስታርስ ቡድንን ከመስርቱት አንዱ ነበር:: ባለፉት 27 አመታት ደግሞ "አጋር" የሚባል ኢትዮጵያ ውስጥ ረዳት የሌላቸውን ተማሪዎች የሚረዳ የረድኤት ድርጅት አቋቁሞ ብዙ ተማሪዎችን እስከዶክተርና ሌሎች ፕሮፌሽናል ዲግሪዎች ድረስ አስተምሯል::

ጋሽ ፍስሃ በሚኖርበት በሎስ አንጀለስ: ካሊፎርኒያ በማህበረሰቡ የተከበረ: ከሁሉም ሰው ጋር መግባባት የሚችል: አገሩንና ህዝቡን የሚወድ: በጋብቻ ከ50 አመታት በላይ የኖረ የሁለት ሴት ልጆች አባት እና የአራት የልጅ ልጆች አያት ነበር:: በፌዴሬሽናችን ስም ለባለቤቱ ለወይዘሮ አልማዝ: ለልጆቹ ለፅዮን እና ናኦሚ እንዲሁም ለመላው ቤተሰቡ: ወዳጅና ዘመዶቹ መፅናናትን እንመኛለን::

የፌዴሬሽናችን አመታዊ ዝግጅት ላይ ግርማ ሞገሳችን መሆንህ በመንፈስ ይቀጥላል:: ፈጣሪ ነፍስህን በእቅፉ ያኑርልን።

"በጎ ስራ የሕይወት ስንቅ ነው!"
የጋሽ ፍስሃ ወልደአማኑኤል የኑሮ መሪ ቃል::